አዲስ አበባ፣ ሐምሌ 22 2002 (ሬዲዮ ፋና) በኢትዮጵያ መንግስትና በተባበሩት የምዕራብ ሶማሌ ነፃ አውጪ ግንባር በቀድሞ መጠሪያው አል ኢትሃድ መካከል የሰላም ስምምነት ተፈረመ።
ስምምነቱን በኢትዮጵያ መንግስት በኩል የፌዴራል ጉዳዮች ሚኒስትር ዶክተር ሽፈራው ተክለማርያምና የተባበሩት የምእራብ ሶማሌ ነጻነት ግንባር ሊቀ መንበር ሸክ ኢብራሂም መሃመድ ፈርመዋል።
ለሰላም ስምምነቱ ኢትዮጵያ ጥረት ስታደርግ መቆየቷን የተናገሩት ሚኒስትሩ ዶክተር ሽፈራው የሰላም ስምምነቱ ለሶማሌ ክልልም ሆነ ለመላው የሃገራችን ህዝብ ጠቀሜታው የጎላ ነው ብለዋል።
የተባበሩት ምእራብ ሶማሊያ ነጻነት ግንባር ለሰላም ያሳየውን ቁርጠኝነትና ሃላፊነት ያደነቁት ዶክተር ሽፈራው ጸረ- ሰላም ዓላማ ይዘው የሚንቀሳቀሱ ሃይሎች ስምምነቱን በአርአያነት ሊወስዱት እንደሚገባም ተናግረዋል።
የግንባሩ ሊቀ መንበር ሸክ ኢብራሂም መሃመድ በበኩላቸው ከጦርነት ይልቅ ሰላምን ምርጫቸው አድርገው ስምምነቱን በመፈረማቸው ደስተኞች መሆናቸውን ጠቅሰው በሶማሌ ክልል እየተካሄደ ባለው ልማትም ከህዝቡ ጎን በመቆም የራሳቸውን አስተዋጽኦ እንደሚያደርጉ ገልጸዋል።